የቤተክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት

ይህ ክፍል ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን፣እንደ አጽዋማት፣ ታላላቅ በዓላት እና የመሳሰሉትን መርሐግብሮች ጊዜውን ጠብቆ ፕሮግራም በማውጣት ሕዝቡን የሚያገለግል ሆኖ በተጨማሪም ልዩ ልዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች ዕለቱንና ሰዓቱን  ጠብቀው እንዲፈጽሙ መዘምራኑን፣ ልዑካኑንና ተጓዳኝ አገልጋዮችን የሚመራና የሚቆጣጠር የመንፈሳዊ አገልግሎት ክፍል ነው፡፡

የቤተክርስቲያኑ ሥዩማን

የቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሕዝቡን በሠለጠነ መንገድ ለማገልገል እንዲቻል የሚከተሉት የቤት ክርስቲያን ሥዩማን አሉት፡፡ ሥራቸውም የቤተ እግዚአብሔር አገልግሎት እንዳይታጎል ካህናትን ሠርተው የሚያሠሩ ናቸው፡፡
እነርሱም፡-

  • 1.    ሊቀጠበብት
  • 2.    ቄሰ ገበዝ
  • 3.    ርዕሰ ደብር
  • 4.    ቀኝ ጌታ ፣ግራ ጌታ ፣ አጋፋሪና
  • 5.    ሊቀ ዲያቆናት እየተባለ በየማዕረጋቸው ይጠራሉ፡፡

ከአጋፋሪና ከሊቀ ዲያቆናት በታች ያሉት ደግሞ መጨኔዎች ሲባሉ የሥርዓተ ማሕሌቱን ዕቃዎች በኃላፊነት ከመጠበቅ ሌላ የምርፋቁ ሥርዓት በአግባቡ እንዲከናወን ተግተው ይሠራሉ (ያሠራሉ)፡፡የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በ  365.5 ቀናት (በ13 ወራት)፣ በ4 ሳምንታትና ከሰኞ እስከ እሁድ ባሉት የሳምንት ቀናት በዓመታዊ በዓላት፣ በአጽዋማት፣ እና በመሳሰሉት ካህናቱን፣ ዲያቆናቱን፣ መዘምራኑንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችን በማስተባበር በሰዓታት፣ በማህሌትና በቅዳሴ ሰፊ አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ከቅዳሴ መሀል ከቅዳሴ ውጭና በቀኑ የጸሎት ሰዓት በተጓዳኝ ሰፊ የወንጌል ስርጭት በመስጠት የስብከት ሥራን በሰፊው ያካሂዳል፡፡

ይህ መንፈሳዊ አገልግሎት ክፍል በባዕዳን እምነት ወጣቱ እንዳይነጠቅ እና ተተኪ የቤተክርስቲያን ተከታዮችን ለማፍራት እንዲቻል የተለያዩ ኮርሶችን በማዘጋጀት ወጣቶችን በእምነት ያንፃል፡፡