የልማት እንቅስቃሴዎች

ካቴድራሉ በልማት በኩል የተከተለው አቅጣጫ

የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በሁሉም አቅጣጫ መሪ እንደመሆኑ መጠንና አስተዳደራዊ ይዘቱም ሰፊ በመሆኑ ገቢው ያኑ ያህል በቂ መሆን ስለሚገባው ከመንግሥት ከተሰጠው ጋሻ መሬት በተጨማሪ ት/ቤት፣ የሙካሽ ሥራ፣ የሥጋጃ ሥራ፣ የአልባሳት ማዘጋጃ፣ የመጻህፍት ማዘጋጃ እና በነዚህ ክፍሎች የተዘጋጁትን የምርት ውጤቶች ለሕዝብ በማቅረብ የሚከፋፈሉባቸው ሱቆች ከአዲስ አበባ እስከ ክ/ሀገር አቋቁሞ ነበር፡፡

ከነዚህ በተጨማሪ ዘመኑ እየሰለጠነ በሄደ መጠን ካቴድራሉ ከህብረተሰቡ የዕድገት ደረጃ ጋር አብሮ እንዲራመድ ከአካባቢው በጣም ዘመናዊና ጠንካራ የሆኑ ሕንፃዎችን አስገንብቶ ከኪራይ በሚያገኘው ገቢ አስተዳደራዊ ዘርፉን ለማስፋፋት ችሎ ነበር፡፡ ፍልውሃ ያለውን ዘመናዊ ሆቴል የራሱ በማድረግ ከቅድስት ሥላሴ ማየ ሕይወትና ከሆቴሉ ከፍ ያለ ገቢ ያገኝ ነበር፡፡ይህ ሁሉ ገቢ በ1966 ዓ.ም. በተደረገው የመንግሥት ለውጥ ካቴድራሉ በማንኛውም የሀገሪቱ ክፍል እንደደረሰው ሁሉ ሀብቱ ሲወረስ ብዙ ገቢ የሚያስገኝለት ት/ቤትም ደረጃው ከ12ኛ ወደ 8ኛ ክፍል ዝቅ እንዲል በመደረጉ የነበረው ፈጣን እንቅስቃሴ ተገታ፡፡
የካቴድራሉ አስተዳደር ጊዜውን ተከትሎ በዘዴ እየተራመደ ት/ቤቱን በወቅቱ አስተዳዳሪ በነበሩት ሊቀሥልጣናት አባ ሀብተ ሥላሴ (ዶ/ር በአቡነ ጢሞቴዎስ) ጥረት ሳይወሰዱ በቀሩት ቦታዎች ምእመናኑን በማደራጀት ሥራው ሳይቋረጥ ሲያዘግም ቆይቶ ቀስ በቀስ የካቴድራሉን ገቢ ሊያዳብሩ የሚችሉ ቋሚ ተግባራትን ሲያከናውኑ እንደነበር ይነገራል፡፡

  • 1.    ሁለገብ አዳራሽ

ይህ አዳራሽ በሊቀ ሥልጣናት አባ ገብረ ማርያም አጽብሐ የተሠራ ሲሆን እጅግ ዘመናዊ እቅድን ተከትሎ የተሠራ ሆኖ ለሠርግ፣ ለስብሰባ፣ ለሙት ዓመት፣ መታሰቢያና ለመሳሰሉት አገልግሎቶች፣ ለአገልጋዮች በነፃ አገልግሎት ሲሰጥ ለውጭ ሰዎች ደግሞ በገንዘብ ይከራያል፡፡ ከአዳራሹ ጋር ተያይዞ የተሠራው የፉካ መቃብርም ለ7 ዓመታት ውል እየተከራየ የካቴድራሉን ገቢ በማሳደግ ላይ ከመሆኑም ሌላ አብሮ የተገነባው ፎቅም ለልዩ ልዩ ድርጅቶች ተከራይቶ ቋሚ ገቢ በማስገኘት ላይ ነው፡፡

  • 2.    ከፍተኛ ክሊኒክ

ይህ ሕንፃ በአንዲት የተከበሩ የቤተክርስቲያን ልጅ ከሆኑት ከወ/ሮ እስከዳር ገ/ሕይወት አስተዋጽኦ ጭምር የተገነባ ዘመናዊ ክሊኒክ ሲሆን ሥራው ተጠናቆና ተመርቆ ካቴድራሉ ለባለሙያዎች አከራይቶት ሥራውን እያካሄደ ይገኛል፡፡

  • 3. ት/ቤት

ሥላሴ ት/ቤት በአንዲት ክፍል በ1955 ዓ.ም. ለካህናት ማሰልጠኛ ተብሎ በማታው ትምህርት ክፍል የተጀመረው ት/ቤት አድጎና ተስፋፍቶ ከላይ እንደተገለጸው ተቋርጦ የነበረው  የ2ኛ ደረጃ ትምህርት በወቅቱ የካቴድራሉ አስተዳዳሪ በነበሩት ሊቀ ሥልጣናት አባ ሐረገወይን ገብረ ሥላሴ /አቡነ ሠላማ/ አስተባባሪነት በማኅበረ ካህናትና በመላው ሠራተኛ ጥረት እጅግ ባማረ እና በተዋበ የተገነባው ሕንፃ ጥቅምት 2ዐ ቀን 1997 ዓ.ም. ተመርቆ ሥራ ላይ ውሏል፡፡ ይህም የሚያሳየው ካቴድራሉ ርእሰ አድባራትና ገዳማት እንደመሆኑ መጠን ሌሎች አብያተክርስቲያናት ፈለጉን ተከትለው ብዙ ሥራዎችን እያከናወኑ በመሆናቸው አሁንም የመሪነቱን ሥፍራ አለመልቀቁን ያሳያል፡፡ ካቴድራሉ በነባሩ ት/ቤት ባለው ሰፊ ቦታ በቅርብ ጊዜ ዘመናዊ ሕንፃ ገንብቶ ኮሌጅ ለመክፍት እቅድ ይዟል፡፡ ይህ ኮሌጅ ሲከፈትም ካቴደራሉ በሁለገብ መልኩ ተጠቃሚ ከመሆኑም ሌላ በውስጡ ያሉ ካህናት፣ መምህራንና ሠራተኞች እውቀታቸውን ይበልጥ እንደሚያሳድጉበት ይጠበቃል፡፡

  • 4. በአሁኑ ወቅትም  በ22 ማዞሪያ ባለ 4 ፎቅ ህንፃ በመሠራት ላይ ይገኛል.