በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ለሥራ ኃላፊዎች የ3 ቀን የምክክርና የግንዛቤ ማስጨባጫ ሥልጠና ተሰጠ

                 “ክፉውን ነገር ተጸየፉት ከበጎ ነገር ጋር ተባበሩ”ሮሜ 12÷9

0003

መልካም አስተዳደር ለዘላቂና ሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት በሚል ርዕስ የተዘጋጀው ሥልጠና የተጀመረው ሐምሌ 9/2005 ዓ.ም ጀምሮ ሲሆን ሥልጠናው እየተካሄደው ያለውም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንገል አዳራሽ ነው፡፡ በዚሁ በዓይነቱ ልዩ የሆነው ሥልጠና ተካፋይ የሆኑ ሥራ ኃላፊዎች፡-

1. የሀገረ ሰብከት ሠራተኞች፣

2. የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ፀሐፊዎች፣

3. የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የሰበካ ጉባኤ ምክትል ሊቃነ መናብርት፣

4. የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የክፍል ኃላፊች፣

5. የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች ናቸው፡፡

ሥልጠናውን በፀሎት የከፈቱት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሲሆኑ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በአ/አ/ሀ/ስ/የቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀጳጳስ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሓፊ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስከያጅ እንዲሁም ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣንት በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ ተገኝተዋል፡፡

የሥልጠናውን መርሃ ግብር የሚመሩት መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስከያጅ ሲሆኑ ከፀሎቱ መርሃ ግብር በኃላ በብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በአ/አ/ሀ/ስ/የቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀጳጳስ አማካኝት ስለ ሥልጠናው አስፈላጊነት በተመለከተ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በመቀጠልም ከመንግስት ተወካይ አጠር ያለ ፀሑፍ ተነቧል፡፡ከዚህ በኋላ ወደ ሥልጠናው የተገባ ሲሆን ሥልጠናው ከፍተኛ ሞያ ባካበቱ በመንግስትና በግል የሚሠሩ ባለሞያዎች ሙሉ ሥልጠናው ተካሂዷል፡፡ተሰብሳቢዎችም ከፍተኛ የሆነ ተሳትፎ አድርገዋል ፡፡

ሥልጠናው በሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት እና በአድባራትና ገዳማት የሚገኙ መሪዎችንና አገልጋዮችን የመሪነትና የሥራ ብቃት ደረጃ ከፍ ለማድረግ ለታሰበው የአሠራር ለውጥ ግንዛቤ ለማስጨበጥ የታቀደ ሥልጠና ነው፡፡ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የፓትርያሪኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ስለ ሥልጠናው ዓላማ አስመልክቶ ሲናገሩ፣ ሀ/ስብከቱ በአስተዳደር፣ በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በማኅበራዊ አገልግሎትና በምጣኔ ሀብት በኩል በሕግና ሥርዐት በመመላለስና በመደራጀት ውጤታማ ሥራ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡ በርካታ ዕቅዶቹን ተግባራዊ ለማድረግ በሀ/ስብከቱ የሚገኙ የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች በለውጡ አጀንዳዎች ላይ በቂ ግንዛቤ እንዲኖራቸው በዘርፉ የላቀ ክህሎትና ዕውቀት ባላቸው ባለሞያዎች የሥልጠናና ምክክር መርሐ ግብሩን ማዘጋጀት አስፈልጓል፡፡

ከሀ/ስብከቱ የሥራ ግዝፈትና ካለው ሰፊ የፋይናንስ ፍሰት አንጻር ሲመዘን ችግሩ የተጋነነና የገዘፈ እንዳልኾነ የሚያምኑት ብፁዕነታቸው፣ ተጠቃሽ ጉድለቶችን ሲዘረዝሩ፡-

1. የመልካም አስተዳደር ግድፈትና ማሽቆልቆል፣

2. ዘመኑን የዋጀ የምጣኔ ሀብት አስተዳደርና ዘመናዊ የሒሳብ አሠራር ክፍተት፣

3. የእርስ በርስ አለመናበብና የጎጠኝነት ስሜት፣

4. ጠንካራ የቁጥጥር ሥርዐት አለመዘርጋት

5. የተአምኖ ግብርና እና የሥነ ምግባር ደረጃ ዝቅ ብሎ መገኘትና የመሳሰሉትን እንደኾኑ ጠቁመዋል፡፡ ብፁዕነታቸው እንዳብራሩት፣ መልካም አስተዳደር÷ ከእግዚአብሔር በተሰጠን ሥልጣንና ሓላፊነት የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት በመስጠት በሁሉም መስክ በጎ አርኣያነት ያለው መልካም እረኛ መኾን ማለት ነው፡፡ በመልካም አስተዳደር መርሕ መሠረት ‹‹ሓላፊ ነኝ፤ አዛዥ ነኝ›› ከሚል መኮፈስ ይልቅ የአገልጋይነትና የመሪነት ስሜት መላበስ ተገቢ ነው፡፡ ‹‹የምንመራትና የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር በደሙ የዋጃት እንደመኾኗ መጠን የተቀበልነው አደራ እጅግ ታላቅና በልዑል እግዚአብሔር ፊት ቀርበን ዋናውን ከትርፍ ጋራ የምንጠየቅበት ነው፤›› ያሉት ረዳት ሊቀ ጳጳሱ፣ የምንመራቸው ሰዎችና የምናስተዳድረው ሀብት የእግዚአብሔር ሀብት ነውና ሓላፊነታችን እጅግ ከባድ እንደኾነና አገልግሎታችንም በዚሁ አቅዋምና መንፈስ ሊቃኝ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ ሐምሌ 9/2005 በተጀመረውና በ11/2005 የሚጠናቀቀው የመጀመሪያው ዙር የሥልጠና መርሃ ግብር፡-

1. መልካም አስተዳደር እና ጠቀሜታው

2. የግዥ ሥርዐት፣ ተያያዥ ችግሮቹና የመፍትሔ አቅጣጫ

3. ዘመናዊ የፋይናንስ አሠራር፣ አያያዝና ተጠያቂነት

4. የዕቅድ፣ ቁጥጥር፣ ክትትል እና ግምገማ ሥርዐት

5. ውጤታማ መሪነት ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ዕድገት

6. ሙስናና ተያያዥ ችግሮች

7. የግጭት መንሥኤ እና አፈታት የሚሉ ርእሰ ጉዳዮች የተካተቱ ሲኾን የዘርፉ ባለሞያዎችና ምሁራን ከቤተ ክርስቲያናችን ተጨባጭ ችግሮች ጋራ በማዛመድ በሚያቀርቧቸው መነሻዎች ተሳታፊዎቹ ውይይት ሰፊ ውይይት አካሂደዋል፡፡ የአሁኑን ጨምሮ በሁለት ዙሮች ከሚካሄደው የሥልጠናና ምክክር ጉባኤ ጋራ በተያያዘ በሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት እና በአዲስ መልክ በተሠራው መዋቅራዊ አደረጃጀት መሠረት በሚቋቋሙት የክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች የሓላፊዎችና ሠራተኞች ምደባ የካሄዳል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ቃል በገባው መሠረት ከሐምሌ 17/2005 በአዲሱ መዋቅር መሠረት ሙሉ ሥራውን ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በአዲሱ አደረጃጀት ሀ/ስብከቱ ለመልካም አስተዳደር በሚያመቹ ሰባት የክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች የተዋቀረ ሲኾን በቋሚ ሲኖዶሱ ተሻሽሎ በጸደቀለት ልዩ መተዳደርያ ደንብ መሠረት በአግባቡና በሥርዓቱ ሥራውን መሥራት ያስችላል ይህ ልዩ ጊዚያዊ መተዳደርያ ደንብ እስከ ጥቅምት ወር ፳፻፮ ዓ.ም ብቻ በጊዜያዊነት የሚያገለግል ሲሆን የሥራ ምደባውም በትምህርት ዝግጅትና በአገልግሎት ዘመን እንደ ሆነ ለማውቅ ተችሏል፡፡ ይህን በተመለከተ ሀገረ ስብከቱ ሥራንና ሠራተኛን ለማገናኘት ትክክለኛውን ሰው በትክክለኛው ቦታ በማስቀመጥ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለው የአሠራር ሂደት በቁርጠኝነት እንደሚከተል የፓትርያሪኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የሥልጠናው መርሐ ግብር ዓላማ ባብራሩበት ወቅት አስረድተዋል፡፡

የኮርሱን ጽሑፍ ዳውንሎድ ያድርጉ (ውጤታማ መሪነት)

የኮርሱን ጽሑፍ ዳውንሎድ ያድርጉ (ሙስና)

{flike}{plusone}

የብፁዕነታቸውን ሙሉ ንግግር ከዚህ ቀጥሉ እንደሚከተለው ይቀርባል

መልካም አስተዳደር ለዘላቂና ሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት

“መኑ እንጋ ገብር ምዕመን ወጢቢብ ዘይሰይም እግዚኡ ውስተ ኩሉ ንዋዩ ከመ የሀቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ . . . ብፁዕ ውእቱ ገብር ዘመጺኦ እግዚኡ ይረክቦ እንዘ ዘንተ ይገብር” “እንኪያስ ምግባቸውን በጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎች ላይ የሾመው ልባምና ታማኝ ባሪያ ማነው? ጌታው መጥቶ እንዲህ ሲያደርግ የሚገኘው ያ! ባሪያ ብፁዕ ነው፡፡” ማቴ.24፡45፡፡

ብፁፁዕ ወቅዱስ አባታችን

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት

ክቡራን እንግዶችና የዚህ አውደ ጥናት ተሳታፊዎች!

በጌታችን በአምላካችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቃል እንደተነገረው፡- የምንመራትና የምናገለግላት ቤተክርስቲያን እግዚአብሔር በገዛ ደሙ የዋጃት መስቀል የተሸከመላትና የተገረፈላት ብዙ መከራ የተቀበለላትና የሞተላት እንደመሆኗ መጠን የተቀበልነው አደራ እጅግ ታላቅና በልዑል እግዚአብሔር ፊት ቀርበን ዋናውን ከትርፍ ጋር የምንጠየቅበት ነው፡፡

የምንመራቸውም ሰዎችና የምናስተዳድረው ሀብት የእግዚአብሔር ሀብት ነውና ኃላፊነታችን እጅግ ከባድ ነው፡፡ በመሆኑም አገልግሎታችን በዚሁ አቅዋምና መንፈስ የተቃኘ መሆን ይገባዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጥንታዊት ታሪካዊት እና ብሔራዊት እንደመሆኗ መጠን ለቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ እድገት አያሌ አስተዋጽኦ ከማበርከቷም በላይ ሕዝቦቿም በማህበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎቶች የተሻለ ሕይወት እንዲኖራቸው ውጤታማ ሥራዎች ሠርታለች እየሠራችም ትገኛለች፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን መሠረታዊ ተልዕኮ ለሰው ልጆች መንፈሳዊና ማሕበራዊ አገልግሎቶችን መስጠት ነው፡፡ ለዚህም ነው ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያለምንም የሃይማኖት፣ የዘር፣ የጾታ ልዩነት ሳታደርግ ከሕዝቦች ሁሉ ጋር ተቀራርባ በመሥራት ሰብአዊ ተግባራትን ስትፈጽም ኖራለች፡፡ በዚሁም ማሕበራዊና የኢኮኖሚ ልማት ማስፋፋት ረገድ የራሷን ልዩ አስተዋጽኦ በማድረግ የሀገሪቱን ልማት በጽኑ የምትደግፍ ብሔራዊት እና ጥንታዊነት ቤተክርስቲያን ናት፡፡

ከማህበራዊ አገልግሎት ባሻገር የትምህርት፣የሥነ ምግባር፣የኪነ ጥበብ፣የሥነ ልሳን ፣የሥነ-ጽሑፍ፣የቅርስና ሌሎችንም አያሌ እሴቶችን ስታስተላልፍ ቆይታለች፣ወደፊትም ትቀጥላለች፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ይህን መልካም ሥራ ለሀገራችን ስታበረክት ያለምንም ፈተና አልነበረም፡፡ በርካታ ፈተናዎች ተገዳድረዋታል፡፡ ሆኖም የሚደርሱባትን ፈተናዎች ሁሉ በብርቱ ታግላ በእግዚአብሔር አጋዥነት ድል አድርጋና ተቋቁማ እነሆ ክብርና ልእልናዋ ተጠብቆ ከዚህ ዘመን ደርሳለች፡፡

የብሔራዊነትና ዓለም አቀፋዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አንድ አካል የሆነው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሀገሪቱ ርዕሰ መዲና እንደመገኘቱና የቤተክርስቲያኗ ዋና የፋይናንስ ምንጭ እንደመሆኑ መጠነ ሰፊ የልማት ሥራ ቢከናወንም አንዳንድ ችግሮች መኖራቸው ግልጽ ነው፡፡ ሀገረ ስብከቱ የአፍሪካ መዲና፣ የዓለም ሀገራት ዲፕሎማቶች መናኸሪያ፣ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መኖሪያ፣ የተለያየ ባሕል ልምድና ፍላጎት መድበል በሆነችው በአዲስ አበባ የሚገኝ እንደመሆኑ፣ እንዲሁም ከሥራው ግዝፈትና ካለው ሰፊ የፋይናንስ ፍሰት አንጻር ሲመዘን ችግሩ የተጋነነና የገዘፈ ነው ተብሎ አይታመንም፡፡ ነገር ግን ያለውን ችግር ስንፈትሽ የተለያዩ ጉድለቶች መኖራቸው እሙን ነው፡፡

ይኸውም ፡ –

1. የመልካም አስተዳደር ግድፈትና ማሽቆልቆል

2. ዘመኑን የዋጀ የምጣኔ ሀብት አስተዳደርና ዘመናዊ የሂሳብ አሠራር ክፍተት

3. የእርስ በእርስ አለመናበብና የጎጠኝነት ስሜት

4. ጠንካራ የቁጥጥር ሥርዓት አለመዘርጋት

5. የተአምኖ ግብርና የሥነ ምግባር ደረጃ ዝቅ ብሎ መገኘትና የመሳሰሉት ተጠቃሽ ናቸው፡፡

ሐዋርያው “በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔር መንጋ ጠብቁ፣ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በውድ እንጂ በግድ ሳይሆን፣ በበጎ ፈቃድ እንጂ መጥፎውን ረብ በመመኘት ሳይሆን ጎብኙት ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ፡፡” 1ጴጥ.5፡2 በማለት እንዳስተማረን መልካም አስተዳደር ከእግዚአብሔር በተሰጠን ሥልጣንና ኃላፊነት ባለን አቅም የምዕመናንን ፍላጎት መሠረት በማድረግ የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት በመስጠት በሁሉም መስክ በጎ አርአያነት ያለው መልካም እረኛ መሆኑን ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በተለይ በሀገረ ስብከቱ እና በሥሩ በሚገኙ አድባራትና ገዳማት ይህ ትርጉም በአብዛኛው የተዛባ ይመስላል፡፡ በመልካም አስተዳደር መርህ መሠረት “ኃላፊ ነኝ፣ አዛዥ ነኝ” ከሚል ስሜት ይልቅ የአገልጋይነትና የመሪነት ስሜት መላበስ ተገቢ ነው፡፡ በአጠቃላይ ሀገረ ስብከቱ በአስተዳደር፣ በፍትህ መንፈሳዊ በማኅበራዊ አገልግሎትና በምጣኔ ሀብት በኩል በሕግና ሥርዓት በመመላለስና በመደራጀት ውጤታማ ሥራ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ወደፊት በርካታ እቅዶች ስላሉት ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ በሥሩ የሚገኙ የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች በጉዳዩ በቂ ግንዛቤ እንዲኖራቸው የላቀ ክህሎትና እውቀት ባላቸው የየዘርፉ ባለሙያዎች ሥልጠና መስጠት በማስፈለጉ ይህንኑ ቅድሚያ ሰጥተን እየሠራን እንገኛለን፡፡

በቀጣይም ልዩ ልዩ የአጭርና የረዥም ጊዜ ሥልጠናዎችን እያዘጋጀን የየአድባራቱን መሪዎችና አገልጋዮች የመሪነትና የሥራ ብቁነት ደረጃ ከፍ እናደርጋለን ብለን እናምናለን፡፡ ከዚሁ ጋር በማያያዝ ሀገረ ስብከቱ ሥራንና ሠራተኛን በማገናኘት ትክክለኛውን ሰው በትክክለኛ ቦታ በመስቀመጥ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ያለው የአሠራር ሂደት በቁርጠኝነት ይከተላል፡፡ ለዚህም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርካችን፣ ቅዱስ ሲኖዶስና የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ከጐናችን እንደሚቆሙ እምነታችን ጽኑዕ ነው፡፡

ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በሚደረገው ሥልጠና እና የምክክር ጉባኤ በርካታ ርዕሰ ጉዳዮች በተለያዩ ምሁራን ይዳሰሳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በመሆኑም የጉባኤው ተሳታፊዎች ይህ መርሃ ግብር የተሳካ እንዲሆን ሁላችሁም የድርሻችሁን እንድትወጡ አደራ እያልኩ ንግግሬን እቋጫለሁ፡፡ የብፁዕ ወቅዱስ አባታችን በረከት ይደረሰን፡፡

ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡