የ2004 የጥምቀት በዓል በካቴድራሉ መሪነት በድምቀት ተከበረ

በመ/ር ዘሩ ብርሃኔ

ጥር 12/2004ዓ.ም

በየዓመቱ ጥር 10 እና 11 የሚከበረው  የጌታችን  የአምላካችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥመቀት በንበረ ፀባኦት ቅድሰት ሥላሴ ካቴድራል መሪነት ከ13 ታቦታት በላይ በሚያድሩበት በጃን ሜዳ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት  የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንትና ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት እንዲሁም በመቶ ሽህ የሚቆጠሩ  ምዕመናን በተገኙበት እጅግ በጣም በደመቀ  ሁኔታ በዓሉ ተከብሮ ውልዋል፡፡

የዓመቱ ተረኛ የሆነው የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን መዘምራን ዕለቱን በማስመልከት ያሬዳዊ ዝማሬ ‹‹ ተሰሃልከ እግዚኦ ምደረከ ሃሌ ሉያ ወረደ ወልድ እም ሰማያት ውስተ ምጥማቃት በፍስሐ ወበሰላም››በማለት ያሬዳዊ ዜማ  አቅርበዋል፡፡

በቤተክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ዐበይት በዓላት ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል የጥምቀት በዓል አንዱ ነው፡፡ይህም በዓል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ ፤ በማእከለ ዮርዳኖስ የተጠመቀበትን  ቅድስት ቤተክርስቲያናችን በየዓመቱ ከዋዜማው ከጥር 10 ጀምሮ በደመቀ ሁኔታ በማክበር ላይ ትገኛለች፡፡ ለእኛ አብነት ይሆነን ዘንድ፤ የእዳ ደብዳቤያችንን እንደ ገል ቀጥቅጦ እንደ ሰም አቅልጦ በደላችንን ይደመስስ ዘንድ ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ይህንን መሠረት በማረድግ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚገኙ ታቦታት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን፣ በካህናትና ዲያቆናት፤ እንዲሁም በሰንበት ት/ቤቶች መዘምራንና ምዕመናን በዝማሬ በመታጀብ በአቅራቢያቸው ወደሚገኘው ታቦት ማደሪያ በማምራት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በመሔድ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ማምራቱን ያበስራሉ፡፡ ‹‹ያን ጊዜም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ናዝሬት መጣ ዮሐንስም በዮርዳኖሰ ወንዝ አጠመቀው›› እንዲል፡፡/ማቴ.3፡1/
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መስራቿን መድኅነ ዓለም ክርስቶስን ለዓለም የምትሰብክበት፣ ከእርሱም ያገኘችውን፣ ይህም ዓለም እንደሚሰጠው ያልሆነውን፣ የእግዚአብሔር ልጅነት፣ ሰላም፣ ፍቅርና ትሕትና ለዓለሙ ትሰብክበታለች፡፡ እንዲሁም ለሀገራችን በጎ ገጽታን በመፍጠር ረገድ ከተለያዩ ሀገራት የሚመጡ ጎብኚዎች ተደንቀው የሚያዩትና አንዳንዶች ልባችውን ለእውነት ክፍት ያደረጉ የሚያምኑበት በመስተንግዶው የሚደመሙበት በመሆኑ ሃይማኖታዊ በዓሉን በልዩ ትኩረት ታከብራለች፡፡

ለዚህ በዓል አከባበር ቤተክርስቲያን ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግ ታቦታት በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲመለሱ ጉልህ ሚናዋን ትወጣለች፡፡ በዚህ መሠረት  በየአጥቢያው የሚገኙ ወጣቶች ከክብረ በዓሉ ቀደም ብሎ ለሐላፊነት በመሰብሰብ ቅዱሳት ሥዕላትን በታቦታት ማረፊያዎች በማዘጋጀት፣ በተለያዩ ህብረ ቀለማት ያሸበረቁ ጨርቆችን /ባነሮችን/፤ የኢትዮጵያ ባንዲራን በየአብያተ ክርስቲያናቱ አደባባዮች በመስቀል፣ የቤተክርስቲያናትን ቅጥርና አስፋልት በማጽዳት ፤ለታቦት ክብርን ለመስጠት ምንጣፎችን በማንጠፍ በዓሉን ያደምቁታል፡፡
ምእመናን ከየቤታቸው ለበዓሉ በሚገባው ልብስ አሸብረቀው ወጥተዋል፡፡ እናቶቻችን ከየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ የሚሰሙትን የሊቃውንት አባቶቻችን ወረብ ተከትልው፣ የታቦታቱን መውጣት በመጠባበቅ እልልታቸውን ያሰማሉ፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችም ዝግጅቶቻቸውን አጠናቅዋል፣ የዝማሬ ልብሳቸውን ለብሰዋል፡፡ የሻሂ የእረፍት ሰዓታቸውን በመጠቀም ከየመሥሪያ ቤታቸው በር ላይ የታቦታትን ማለፍ በእነርሱም መባረክን ዓይናቸው ተስፋ እያደረገች ታቦታቱ የሚመጡበትን አቅጣጫ ያማትራሉ፡፡
ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር በተለይም በጃንሜዳ ከየአድባራቱ አስራ ሦስት ታቦታት በአንድነት የሚገኙበት በመሆኑ ህዝቡን ለመባረክ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተ/ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሐይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ከብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን፤ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ልብሰ ተክህኖ ለብሰው ፤በመዘምራንና ምዕመናን በመታጀብ ጉዞ የተጀመረ ሲሆን አመሻሽ ላይ ጃን ሜዳ ሊደርሱ ችለዋል፡፡ የየሰንበት ት/ቤቶቹ መዘምራን ፤ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዜማ እየዘመሩ ፤ምዕመናን በዕልልታና በሸብሸባ ታቦታቱን በማጀብ በዓሉን አድምቀውታል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከጋዜጠኞች ለቀረበ ጥያቄ እለቱን በማስመልከት በሰጡት መግለጫ ‹‹የዛሬው በዓላችን በሃይማኖታችን ውስጥ የእግዚአብሔርን ጸጋና በረከት የምናገኝበት፤ ሁላችንም በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የምንወለድበት፤ ልጅነት የምናገኝበት በዓል ነው፡፡›› በማለት  ገልጸዋል፡፡

በበዓሉ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ከውጭ ሀገር በዓሉን ለመከታተል የመጡ እንግዶችና ቱሪስቶች የተገኙ ሲሆን   በብጹዕ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ገሪማ ሰፋ ያለ  ቃለ እግዚአብሔር  ተሰጥቷል፡፡ በመጨረሻም በብጹዕ አቡነ ጳውሎስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቦታ ገብተዋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር