የብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ የ1ኛ ዓመት መታሰቢያ የፀሎት ስነ ሥርዓት ተካሄደ

0021

ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ የተለዩት የ5ኛው ፓትርያርክ የብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዝደንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት ኅልፈት የአንደኛ ዓመት መታሰቢያ ሥነ ሥርዐት ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በማሕሌት፣ በጸሎተ ፍትሐትና በቅዳሴ ታስቦ ውሏል፡፡በመታሰቢያ ክብረ በዓሉ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ፤ ካህናትና ምእመናን የተገኙ ሲሆን በቅዱስነታቸው መሪነት ሙሉ ፀሎተ ፍትሐት ከደረሰ በኋላ ከሰዓት ፀሎተ ቅዳሴው ተከናውኗል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በ20 ዓመት የፕትርክና ዘመናቸው ለሀገራቸውና ለዓለም ያበረከቱት አስተዋፅኦ ከፍተኛ እንደነበር በዚሁ የመታሰቢያ መርሃ ግብር ላይ ተገልጿል፡፡ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የአንደኛ ዓመት መታሰቢያ የፀሎት ስነ ሥርዓት በመንበረ ጸባዖት ቅድስተ ሥላሴ ካቴድራል ባለው መካነ መቃብራቸው ላይ ተካሂዷል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሐምሌ 1984 ዓ.ም ፓትሪያሪከ ሆነው ከተሾሙበት ጊዜ አንስቶ ለሀገር እድገትና ልማት ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማበርከት ለ20 ዓመታት ሐወርያዊ ተልእኳቸውን በመፈፀምና ከፍተኛ አገልግሎት በማበርከት ለቅድስት ቤተክርስትያንና ለሀገሪቱ ታላላቅ ሥራዎችን ሰርተው ማለፋቸው ተገልጿል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትርያርክ በስነ ሥርዓቱ ላይ እንደገለፁት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ በህይወት ዘመናቸው ለትምህርት መስፋፋት፣ ለሀገርና ለዓለም ሰላም እንዲሁም የኃይማኖት መቻቻልንም በሰፊው በማስተማርና በቤተክርስትያኗ ለሀገር እድገት ጉልህ አስተዋፅኦ እንድታበረክት በማስቻል ከፍተኛውን ሚና ያበረከቱ እንደነበር ገልፀዋል፡፡

በተያያዘ ዜና የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አንደኛ ዓመት መታሰቢያ ስነ ሥርዓት ነሐሴ 14/2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ባለው መካነ መቃብሩ ተካሂዷል፡፡በመታሰቢያ ክብረ በዓሉ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፤ የኢፌድሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ሚኒስትሮች፤ ክብርት ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን ፤ ካህናትና ምእመናን በታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ መካነ መቃብር በፀሎቱ መርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል፡፡ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በመታሰቢያ የፀሎት መርሐ ግብሩ ላይ ለተገኙ ምዕመናን ሠፊ የሆነ ትምህርተ ወንጌል ሠጥተዋል ፡፡

00020

{flike}{plusone}